ኦሊሴ በሃያላን ክለቦች መካከል ከፍተኛ የዝውውር ፍልሚያ ቀሰቀሰ
የጥር የዝውውር መስኮት መከፈቻ እየተቃረበ ባለበት በዚህ ወቅት፣ ማይክል ኦሊሴ በታላላቅ ክለቦች ዘንድ በከፍተኛ ሁኔታ ከሚፈለጉ ተጫዋቾች መካከል አንዱ ሆኖ ብቅ ብሏል። ሪያል ማድሪድ፣ ማንችስተር ሲቲ እና ሊቨርፑልም ይህን የባየር ሙኒክ የክንፍ መስመር ተጫዋች በቅርብ እየተከታተሉት ይገኛሉ። ይህ ፈረንሳዊ ኢንተርናሽናል በጀርመን ቦንደስሊጋ በዘንድሮው የውድድር ዘመን ባደረጋቸው 23 ጨዋታዎች ብቻ 9 ግቦችን አስቆጥሮ 11 የግብ ዕድሎችን በመፍጠር ድንቅ ብቃቱን እያሳየ ይገኛል። እንደ ዘገባዎች ከሆነ ሊቨርፑል ኦሊሴን የመሀመድ ሳላህ የረጅም ጊዜ ተኪ አድርጎ ሲመለከተው፣ ሲቲ እና ማድሪድ ደግሞ ወዲያውኑ ውጤት ሊያመጣ የሚችል ድንቅ የአጥቂ መስመር አማራጭ አድርገው ይቆጥሩታል።
ይሁን እንጂ ማንኛውም ዓይነት የዝውውር ስምምነት ቀላል የሚሆን አይደለም። ኦሊሴ ከባየር ሙኒክ ጋር እስከ 2029 የሚያቆይ ውል ያለው በመሆኑ፣ የጀርመኑ ሻምፒዮን ክለብ እጅግ ከፍተኛ የሆነ የዝውውር ሂሳብ ካልቀረበለት በስተቀር ተጫዋቹን ለመሸጥ ምንም ዓይነት አስገዳጅ ጫና የለበትም።
የማንቸስተር ዩናይትድ የመሃል ክፍል አጣብቂኝ
ብራይተኖች ከማንቸስተር ዩናይትድ በኩል ቀጣይነት ያለው ፍላጎት ቢኖርም፣ ለካርሎስ ባሌባ የሚቀርቡ የዝውውር ጥያቄዎችን ቢያንስ እስከ 2027 ድረስ እንደማይቀበሉ ግልጽ አድርገዋል። የ21 ዓመቱ ተጫዋች በኦልድ ትራፎርድ የረጅም ጊዜ የዝውውር ዕቅድ ውስጥ ቢገኝም፣ ዩናይትዶች ግን አሁን ላይ ሌሎች አማራጮችን መመልከት ጀምረዋል።
ዩናይትድ በመሃል ክፍሉ ላይ በርካታ ማጠናከሪያዎችን ለማድረግ ባቀደው መሠረት፣ የክሪስታል ፓላሱ አዳም ዋርተን እና የኖቲንግሃም ፎረስቱ ኤሊዮት አንደርሰን በክለቡ የእጩዎች ዝርዝር ውስጥ ተካተዋል። ክለቡ ቀዳሚ ምርጫዎቹ የሆኑ ተጫዋቾችን ማስፈረም አለመቻሉ፣ የዝውውር ስልቱን በየጊዜው እንዲቀያይር እያገደደው ይገኛል።
አስቶን ቪላ ስለ ቴር ስቴገን ዝውውር የመጀመሪያ ጥያቄውን አቀረበ
አስቶን ቪላ የኤሚሊያኖ ማርቲኔዝ ተደጋጋሚ የጀርባ ህመም አሳሳቢ እየሆነባቸው በመምጣቱ፣ ማርክ-አንድሬ ቴር ስቴገንን ለማስፈረም ለባርሴሎና የመጀመሪያ ጥያቄያቸውን አቅርበዋል። ይህ የጀርመን ብሔራዊ ቡድን ግብ ጠባቂ የዓለም ዋንጫ ከመድረሱ በፊት በቋሚነት የመሰለፍ ዕድል ለማግኘት ይፈልጋል፤ ተጫዋቹን ለማስፈረምም ከቪላ በተጨማሪ ጂሮና እና የሳውዲ ፕሮ ሊግ ክለቦች ፍላጎት አሳይተዋል።
ባርሴሎና እስካሁን ግልጽ የሆነ ይፋዊ አቋም ባያሳውቅም፣ አስቶን ቪላዎች ግን የ33 ዓመቱ ግብ ጠባቂ በከፍተኛ የፉክክር ደረጃ ላይ ፈጣን መረጋጋትን ሊፈጥር እንደሚችል ያምናሉ።
የተጫዋቾች ውሰት፣ ስንብቶች እና የምናውቃቸው ፊቶች
ሪያል ማድሪድ በአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን የዓለም ዋንጫ ዕቅድ ውስጥ ለመካተት በቋሚነት የመጫወት ፍላጎት ላለው ታዳጊ አማካኝ ፍራንኮ ማስታንቱኖ፣ በጥር የዝውውር መስኮት የውሰት ዝውውር ለማመቻቸት እያሰቡ ነው። ሆኖም “ሎስ ብላንኮዎቹ” ተጫዋቹን በቋሚነት የመሸጥ ምንም ዓይነት ፍላጎት የላቸውም።
የጃደን ሳንቾ የወደፊት ቆይታ አሁንም እርግጠኛ ባልሆነ ሁኔታ ላይ ይገኛል። ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ለሶስተኛ ጊዜ ተጫዋቹን መልሶ ለማግኘት ጥረት እያደረጉ ሲሆን፣ ሞናኮ እና ኮሞም ከተጫዋቹ ወኪሎች ጋር ንግግር አድርገዋል። ማንቸስተር ዩናይትድ ተጫዋቹን በድጋሚ ከቡድኑ ጋር የመቀላቀል እቅድ የሌላቸው ሲሆን፣ አስቶን ቪላ ደግሞ ተጫዋቹ አሁን ያለበትን የውሰት ጊዜ እዚያው ሆኖ እንዲያጠናቅቅ ይፈልጋሉ።
በዝምታየተጀመሩእንቅስቃሴዎችፍጥነታቸውንእየጨመሩነው
በሌላ በኩል፣ አንትዋን ሴሜንዮ ከማንቸስተር ሲቲ ይልቅ ለሊቨርፑል ቅድሚያ እየሰጠ ይገኛል፤ ባየር ሙኒክ እና ዶርትሙንድ ደግሞ ፍራንኩሊኖ ጁን በቅርብ እየተከታተሉ ነው። ኤሲ ሚላን በበኩላቸው ኒክላስ ሱለን በነፃ ዝውውር ለማስፈረም ዓይናቸውን ጥለውበታል። የጥር የዝውውር መስኮት እየተቃረበ በመምጣቱ፣ በርካታ የአውሮፓ ክለቦች ቀደም ብለው ዝግጅታቸውን በማጠናቀቅ ላይ ይገኛሉ።

