ፊፋ ከደጋፊዎች በተነሳበት ከፍተኛ ተቃውሞ ምክንያት የዓለም ዋንጫ የትኬት ዋጋን ቀነሰ
ለታማኝ ደጋፊዎች የ60 ዶላር ትኬቶች ቀረቡ
ፊፋ በዓለም አቀፍ ደረጃ የደረሰበትን ከፍተኛ ተቃውሞ ተከትሎ ውስን የሆኑ የዓለም ዋንጫ ትኬቶችን ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል፤ በዚህም መሰረት የተወሰኑ ደጋፊዎች የፍፃሜውን ጨዋታ ጨምሮ ሌሎች ጨዋታዎችን እስከ 4,185 ዶላር ይከፈልባቸው ከነበሩ ወንበሮች ይልቅ በ60 ዶላር ብቻ የመታደም ዕድል ያገኛሉ።
የእግር ኳስ የበላይ አካሉ (ፊፋ) እንደገለጸው፤ በሰሜን አሜሪካ በሚካሄደው የ2026 ዓለም ዋንጫ ላይ ለሚደረጉ እያንዳንዱ ጨዋታዎች በ60 ዶላር የሚሸጡ ትኬቶች በአዲሱ “የደጋፊዎች መግቢያ ደረጃ” አማካኝነት ይቀርባሉ። እነዚህ ትኬቶች ለየሀገራቱ የእግር ኳስ ፌዴሬሽኖች የሚከፋፈሉ ሲሆን፤ ፌዴሬሽኖቹም ቡድኖቻቸውን በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር በቋሚነት ለሚከተሉ ታማኝ ደጋፊዎች እንዴት እንደሚሰጡ ውሳኔ ያስተላልፋሉ።
ውስን አቅርቦት እና ተምሳሌታዊ ለውጥ
የዋጋ ቅናሽ የተደረገባቸው ትኬቶች ቁጥር በጣም ውስን እንደሚሆን የሚጠበቅ ሲሆን፤ ይህም ለእያንዳንዱ ጨዋታ በሺዎች የሚቆጠር ሳይሆን በመቶዎች የሚገመት ብቻ ሊሆን ይችላል። ፊፋ እንዳረጋገጠው ከሆነ፤ ለብሄራዊ ማህበራት ከሚሰጡት አጠቃላይ ትኬቶች ውስጥ 10 በመቶው ብቻ በ60 ዶላር ምድብ ውስጥ ይካተታሉ። ብሄራዊ ማህበራቱ ደግሞ በራሳቸው ለእያንዳንዱ ጨዋታ ከሚቀርቡት ጠቅላላ ትኬቶች ውስጥ 8 በመቶ ድርሻ ብቻ ነው ያላቸው።
ለፍፃሜው ጨዋታ ለተፋላሚ ሀገራት ከሚሰጡት በግምት 4,500 ትኬቶች ውስጥ 450 ያህሉ ብቻ በቅናሽ ዋጋ የሚቀርቡ ይሆናሉ። ፊፋ ይህ የዋጋ ለውጥ ከደጋፊዎች በደረሰበት ተቃውሞ ምክንያት ስለመሆኑ በግልጽ ባያምንም፤ አዲሱ የዋጋ ተመን “በውድድሩ ወቅት ብሄራዊ ቡድኖቻቸውን ተከትለው ለሚጓዙ ደጋፊዎች ተጨማሪ ድጋፍ ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ ነው” ብሏል።
በትኬት ዋጋ መመሪያው ላይ የተቀሰቀሰ ከፍተኛ ቁጣ
ይህ እርምጃ የተወሰደው ፊፋ ቀደም ሲል ባወጣው እና ተሳታፊ የሆኑ የሀገራት ደጋፊዎችን በዝቅተኛ የዋጋ ምድብ ውስጥ ያላካተተውን የትኬት ሽያጭ ስትራቴጂ ተከትሎ በደረሰበት ከፍተኛ ትችት ምክንያት ነው። በምድብ ጨዋታዎች ወቅት አስተናጋጅ ያልሆኑ ሀገራት ጨዋታዎች ዋጋ ከ120 እስከ 265 ዶላር ተመን ወጥቶላቸው የነበረ ሲሆን፤ ቡድኖቻቸውን ተከትለው እስከ ፍፃሜው ድረስ መጓዝ ለሚፈልጉ ደጋፊዎች ደግሞ ወጪያቸው ከ7,000 ዶላር በላይ ሊደርስ ይችል ነበር።
ውዝግቡ ይበልጥ የከረረው “ዳይናሚክ ፕራይሲንግ” (እንደ ፍላጎቱ የሚዋዥቅ ዋጋ) እና ተጨማሪ የትኬት ዳግም ሽያጭ ክፍያዎች በመተዋወቃቸው ነው። እነዚህ አሰራሮች በአሜሪካ የመዝናኛ ዘርፍ የተለመዱ ቢሆኑም፤ በዓለም ዙሪያ በሚገኙ የእግር ኳስ ደጋፊዎች ዘንድ ግን የማይታወቁና ተወዳጅነት የሌላቸው ናቸው።
የተሰጡት ምላሾች አሁንም ድብልቅ ስሜት የሚታይባቸው ናቸው
“ፉትቦል ሳፖርተርስ ዩሮፕ” (FSE) የተሰኘው የደጋፊዎች ቡድን የቀረበውን መግለጫ በበጎ ቢቀበለውም፣ ለአካል ጉዳተኛ ደጋፊዎች እና አብረዋቸው ለሚጓዙ ረዳቶች የሚሆን ግልጽ የዋጋ አወቃቀር ባለመኖሩ ውሳኔው በቂ አይደለም ብሏል። ድርጅቱ ለውጦቹን “ደጋፊዎችን ለማስታገሻነት የቀረበ ዘዴ” በማለት የገለጸው ሲሆን፣ ከደጋፊዎች ጋር ትርጉም ያለው ውይይት እንዲደረግም ጥሪ አቅርቧል።
የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ኪር ስታርመርም ፊፋ ተጨማሪ ማሻሻያዎችን እንዲያደርግ ያሳሰቡ ሲሆን፤ የትኬት ዋጋ ተመጣጣኝ ካልሆነ የዓለም ዋንጫው ከእውነተኛ ደጋፊዎች ጋር ያለው ግንኙነት ሊቋረጥ እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል።
ፊፋ የአሰራር ሞዴሉን ተከላክሏል
ፊፋ ከውድድሩ የሚገኘው ገቢ በ211 አባል ማህበራቱ አማካኝነት ለዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ልማት በድጋሚ ስራ ላይ እንደሚውል አፅንዖት ሰጥቶ ገልጿል። በተጨማሪም ከፍፃሜው ጨዋታ በኋላ ለሚደረጉ የትኬት ገንዘብ ተመላሾች ምንም ዓይነት የአስተዳደር አገልግሎት ክፍያ እንደማይጠየቅ አረጋግጧል።የመጨረሻው የሽያጭ ምዕራፍ ከተከፈተ ጀምሮ ከ20 ሚሊዮን በላይ የትኬት ጥያቄዎች የቀረቡ ሲሆን፤ ትኬት የደረሳቸው አመልካቾች እስከ የካቲት ወር 2026 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) ድረስ ማሳወቂያ ይላክላቸዋል።

